| የቻይናው ሲአርቢሲ በክፍያ ምክንያት ሥራ ሊያቆም መሆኑን አስታወቀ |
|
|
|
| Written by solomon | |||
| Monday, 28 June 2010 16:00 | |||
|
በመንገድና በድልድይ ግንባታ የሚታወቀው የቻይናው ኩባንያ (ሲአርቢሲ) ገንብቶ ለጨረሳቸውም ሆነ ወደ ፊት ለሚገነባቸው መንገዶች ክፍያ ስላልተፈጸመለት፣ ከሐምሌ 15 ቀን 2002 ዓ.ም. ጀምሮ ሥራ እንደሚያቆም ለአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር በጻፈው ደብዳቤ አስጠነቀቀ፡፡ለ2003 በጀት ዓመት ከሚጸድቀውና በሐምሌ ወር ከሚሰበሰበው ገቢ ክፍያውን ለመፈጸም በካቢኔ መወሰኑን፣ ስማቸው እንዲገለጽ ያልፈለጉ የካቢኔው አባል ለሪፖርተር አሳውቀዋል፡፡
ኩባንያው በሦስት ቁጥር ማዞርያ፣ በፑሽኪን አደባባይ፣ በመገናኛ፣ በቀበናና በሌሎችም አካባቢዎች ያሉ መንገዶችን ቢያጠናቅቅም፣ አስተዳደሩ ባጋጠመው የበጀት እጥረት ምክንያት ክፍያውን ሊፈጽምለት ባለመቻሉ ደብዳቤ ለመጻፍ መገደዱን ኃላፊው ገልጸዋል፡፡
ሲአርቢሲ መንገዶችን ለመገንባት ከአስተዳደሩ ጋር ሲፈራረም መንገዱ የሚፈጀውን የግንባታ ወጪ 20 በመቶ ከተከፈለው በኋላ፣ ግንባታውን ደረጃ በደረጃ ሲጨርስና በአማካሪ መሐንዲስ ሲረጋገጥ ተጨማሪ ክፍያ እንደሚከፈለው ቢስማማም፣ አስተዳደሩ አጋጥሞኛል በሚለው የበጀት እጥረት ምክንያት እስካሁን ያልተከፈለው ከ200 ሚሊዮን ብር በላይ እንዳለውና በደብዳቤ መጠየቁን ኃላፊው አረጋግጠዋል፡፡
ኩባንያው ካለፉት ሁለት ሳምንታት ጀምሮ በርካታ ሠራተኞችን በሁለት ምክንያቶች መቀነሱን የገለጹት ኃላፊው፤ አንደኛው በተወሰኑ አካባቢዎች የሚሠራቸው ሥራዎችን በማጠናቀቁ ሲሆን፣ ሁለተኛው ደግሞ አስተዳደሩ ክፍያ ካልፈጸመለት መክፈል ስለማይችል መሆኑን ተናግረዋል፡፡
በኩባንያው የሥራ ኃላፊ በአቶ ዘየደ ተስፋዬ ፊርማ ከሥራ የተሰናበቱት ሠራተኞች ያለምንም ቅድመ ሁኔታ ሥራ በማቆማቸው ግራ መጋባታቸውንና የቤተሰብ አስተዳዳሪ በመሆናቸው ምን ማድረግ እንዳለባቸው እንደማያውቁ ተናግረው፣ የአሠሪና ሠራተኛ አዋጅ በሚያዘው መሠረት የሞራል ካሣ ክፍያ፣ የአገልግሎትና የመሳሰሉትን ክፍያዎች ፈጽሞ እንዲያሰናብታቸው እየጠየቁ መሆኑን ገልጸዋል፡፡
የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር ካቢኔ አባል የሆኑና ስማቸውን መግለጽ ያልፈለጉ አንድ ኃላፊ እንደገለጹት፤ አስተዳደሩ አጋጠመው የተባለው የበጀት ችግር እውነት መሆኑንና አስተዳደሩም የኩባንያውን ጥያቄ መቀበሉን፤ ከ2003 ዓ.ም. በጀት ከሐምሌ ወር ጀምሮ ከሚሰበሰበው ገቢ ለኩባንያው በቅድሚያ እንዲከፈለው በካቢኔ መወሰኑን አስረድተዋል፡፡
ከአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደር የኮሚዩኒኬሽንና ሕዝብ ግንኙነት የሥራ ሒደት ኃላፊዎች ምላሽ ለማግኘት ያደረግነው ሙከራ አልተሳካልንም፡፡
ሪፖርተር
|
|||
| Last Updated on Monday, 28 June 2010 16:12 |
Add your comment
ADD
Comments, category: "amharic"
- የአዲስ ነገር ጋዜጣ አዘጋጆች ሕትመቱን አቋርጠው ተሰወሩ (4)
- እኛ ካላሸነፍን ምርጫው መጭበርበሩ ይታወቃል ሲሉ የአንድነት አመራሮች አስታወቁ (2)
- አቶ ስዬ አብርሃ መንታ መንገድ ላይ መቆማቸው ታወቀ (1)
- ከአፄው ስርዓት ጋር የሚመሳሰል የምርጫ ቅስቀሳ በተምቤን ተጀመረ (1)
- ኢትዮጵያ ግብረ-ሰዶም ባለመፍቀዷና ግልገል ጊቤን በማልማቷ ሁማን ራይትስ ዎች ከሰሰ፤ አቶ ገብሩ አስራትና አቶ ቡልቻ ደመቅሳ በምንጭነት ተጠቅሰዋል (1)
- የኢ/ጉ/ገ/ ባለሥልጣን 6 ህገ ወጥ ነጋዴዎች ወደ ህግ ማቅረቡን አስታወቀ (1)












